አካል ጉዳት እና ግንዛቤው
- Zebeaman Tibebu
- Mar 12
- 4 min read
Updated: Mar 17
አያድርገውና...

ድንገት ባልታሰበ አጋጣሚ፤ ህይወቶት በቅጽበት ቢለወጥስ?
አሁን በነጻነት የሚያድርጓቸውን ተግባሮች ማድረግ ቢሳኖትስ?
ያጋጠሞት አካላዊ ጉዳት ጉዳት የእርሶ ማንነት ላይ ለውጥስ ይኖረው ይሆን ?
ይህ የብዙ ሰዎች ነባራዊ እውነታ ነው። በመኪና አደጋ ወይም በስራ ቦታ ላይ ባጋጠመ አደጋ ፤ አካል ጉዳተኛ ሆነው ህይወትን እየመሩ ያሉ ግለሰቦች ጥቂት አይደሉም። የአለም ጤና ድርጅት እንደ ኤሮፕያውያን አቆጣጠር በ 2023 ያወጣው መረጃ እንደሚያመላከተው ፤ ከ አለም ህዝብ ውስጥ 16 ፐርሰንት የሚሆኑ (1.3 ቢሊየን ሰዎች) የአካል ጉዳተኝነት ጋር ይኖራሉ።
በኢትዮጵያ አሁን ያለውን መጠን የሚያሳይ መረጃ ባይኖርም ከ ሰባት አመት በፊት ዩኒሴፍ ያወጣው መረጃ 9.3 ፐርሰንት የሚሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ የአካል ጉዳተኝነት እንዳለበት ያሳያል። ለዚህም ዋነኛ መንስኤዎቹ አደጋ እና ግጭት ናቸው።
በአለም ላይ በ አመት ወደ 4.4 ሚሊየን ህዝብ በ አደጋ እና በግጭት መንስኤ ህይወቱ ያልፋል። ከዚህ ውስጥ አንድ አራተኛው በመኪና አደጋ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ በየአመቱ ወደ አራት ሺህ የሚገመት የመኪና አደጋ እንደሚያጋጥም ጥናቶች ያመላክታሉ። በኮንስትራክሽን ስራ ላይ ከተሰማሩ ሰራተኖች ውስጥ እስከ ሀምሳ ፐርሰንት የሚሆኑት በስራ ቦታቸው ላይ ለአደጋ ይጋለጣሉ።
ታድያስ የአካል ጉዳት ምንድነው?
የአካል ጉዳት ምንድን ነው?

ማንኛውንም አካላዊ፣ አእምሮአዊ፣ ባህሪያዊ እክል የአንድ ሰው የዕለት ተዕለት ተግባሩን የማከናወን ችሎታውን የሚፈታተን ከሆነ አካልጉዳት ተብሎ ይጠራል። በተጠቃው ኣካል ላይ ተመስርቶ የተለያዩ የአካል ጉዳት አይነቶች ቢኖሩም ስለ ሶስቱ እንወያይ።
አካላዊ የአካል ጉዳተኝነት (Physical Disability)
ከቦታ ቦታ በነጻነት የመንቀሳቀስ ችሎታን ብዙ ሰው አቅልሎ ቢመለከተውም ፤ አካላዊ የአካል ጉዳተኝነት ላለባቸው ሰዎች ይህ ድርጊት ፈታኝ ይሆንባቸዋል። አካላዊ አካል ጉዳተኝነት ያለባቸው ሰዎች አንድ ወይም ከዚያ በላይ ያለ የሰውነት ክፍላቸው (በተለይም ለመንቀሳቀስ የሚጠቀሙት የሰውነት ክፍል) በሙሉ አቅሙ መስራት የተሳነው ይሆናል።
ይህም በተለያየ ምክንያት ሊከሰት ይችላል። በአደጋ፣ በግጭት እንዲሁም በበሽታ ሊመጣ ይችላል። ከ ዘረመል ጋር በተያያዙ ምክንያቶች እንዲሁም ከወሊድ ጋር በተያያዙ ችግሮችም ሊፈጠር ይችላል።
ኢትዮጵያ ላይ የተደረገው ሀገር አቀፍ የፖሊዮ ክትባት ፤ ህመሙን ተከትሎ የሚመጣው የአካል ጉዳተኝነት መጠን እንዲያሽቆሎቁል አድርጎታል። ሆኖም ግን በመኪና አደጋ እና በግጭት ምክንያት የሚያጋጥሙት አካላዊ ጉዳቶች መጠናቸው አልቀነሰም። ከዚህም ባሻገር ስኳር፣ ውፍረት፣ ደምግፊትን ተከትሎ የሚመጡ አካላዊ ጉዳቶች እየጨመሩ ይገኛሉ።
አሁን ባለንበት እርስ በእርስ ግጭትስ ስንት ሰው አካልጉዳተኛ እየሆነ ይገኛል? ደብቀን የምናስታምማቸውስ ምን ያህል ይሆኑ?
ደግነቱ አሁን ያለንበት የህክምና እና የቴክኖሎጂ ልህቀት ለብዙዎቹ ህይወታቸውን አሻሽሏል እያሻሻለም ይገኛል። ከተሽከርካሪ ወንበር ጀምሮ፣ አርተፍሻል አካላት (ፕሮስተቲክስ) እንዲሁም የ ፊዚዮቴራፒ ህክምና የመንቀሳቀስ ነጻነታችውን የመለሰላቸው ጥቂት አይደሉም። በዚህም የተነሳ ራስን በራስ የመመራትና በራስ የመተማመን ስሜታችውም አብሮ እየጎለበተ ይገኛል።
የስሜት ህዋሳት አካል ጉዳተኝነት (Sensory Disability)
ሌላኛው የአካል ጉዳተኝነት አይነት የስሜት ህዋሳትን የሚያካትት የአካል ጉዳተኝነት ነው። ይህም ያሉን የስሜት ህዋሳት ሙሉ ስራቸውን መስራት ሲሳናቸው የሚያጋጥም ነው። የስሜት ህዋሳት በዙሪያችን ካለው አለም ጋር የምንግባባችው በመሆናቸው፤ በሙሉ አቅም አለመስራታቸው አከባቢያችንን በሙሉ ደረጃ እንዳናጤን ያደርጋል። እንደተጠቃው የስሜት ህዋስ አካልጉዳተኝነቱ ቢለያይም፤ ከሌሎች ሰዎች ጋር ያለ ግንኙነት ላይ ተጸዕኖ ሊያሳደር ይችላል። ሆኖም ግን ሁልጊዜ በቀላሉ ላይታወቅ ይችላል። እንደ ከለር አለማየት፤ የማሽተት አለመቻል የመሳሰሉት የአካል ጉዳተኝነት አይነቶች ሳይታወቁ ረዝም ጊዜ ሊቆዩ ይችላሉ።
ይህም አካል ጉዳተኝነት በተለያየ ምክንያት ሊመጣ ይችላል። በኢትዮጵያ ውስጥ ትራኮማ እና የአይን ሞራ ግርዶሽ ለስውርነት የሚያጋልጡ ዋነኛ መንስኤዎች ናቸው። በመታከም ሊድኑ የሚችሉ ቢሆኑም፤ በህክምና እጦት ወይም በንጽህና አጠባበቅ ጉድለት አይን ሊያጠፉ ይችላሉ። በጊዜው ያልታከመ የጆሮ/ጉሮሮ አከባቢ ኢንፌክሽን ህመሞች በበኩላቸው የመስማት ችግርን ሊያመጡ ይችላሉ። ከዚህም ባሻገር ከማይተላለፉ ህመሞች (ነን ኮምኑዩኬብል ዲዚስ) ተያይዞ ሊመጣ ይችላል። ለዚህም ነርቭ ላይ በሚያመጣው ለውጥ የመዳሰስ ችግርን በማስከተል ፤እንዲሁም አይን ላይ በሚያደርሰው ጥቃት ለአይነስውርነት በመዳረግ፤ የስኳር ህመም ተጠቃሽ ነው። በእርግዝና እና በወሊድ ጊዜ በሚያጋጥሙ ችግሮችም ሊከሰት ይችላል።
መልካሙ ነገር አስፈላጊውን ህክምና በጊዜው በማድረግ አብዛኛውን መከላልከል ይቻላል። የተቀሩትን በ ህክምና እገዛ ሊደገፉ ይችላሉ። እንደ ኮችሊያር ኢምፕላንት፣ የሌንስ መተካት፣ የእይታ መነጽር ማድረግ፤ የጨረር የአይን ህክምና ያሉ የህክምና አማራጮች ሕይወታቸው ላይ ትልቅ እመርታ ያመጣሉ። በተጨማሪም በአለም ዙሪያ የምልክት ቋንቋ እና ብሬይል እየተስፋፉ በመምጣታቸው የአካል ጉዳተኝነት የሌለበት የማህበረሰብ ክፍልም እየተማራቸው ይገኛል። ብዙ ኢትዮጵያዋያን በጉዳዩ ግንዛቤ በመምጣታቸው የተሻለ የማህበረሰብ ድጋፍ እያገኘ ነው።
አእምሮአዊ የአካል ጉዳት (Cognitive Disability)
ይህም የአካል ጉዳት አእምሮ በደንብ ሳይጎለብት ሲቀር ወይም አእምሮ ውስጥ ያሉ የመግባቢያ ኬሚካሎች ላይ መዛባት ሲያጋጥም የሚፈጠር የአካል ጉዳተኝነት ነው። በዚህም የተነሳ ነገሮችን የመገንዘብ ችሎታቸው የተለወጠ ይሆናል። እንደ ዳውን ሲንድሮም፣ ኢንቴሌክቿል ዲሴቢሊቲ፣ ኦቲዝም የመሳሰሉ ህመሞች እዚህ ውስጥ ይካተታሉ።
በእርግዝና ወራት ባለ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት፣ በእርግዝና ወቅት የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች( ለምሳሌ፡ ሩቤላ፣ ወባ፣ ወ.ዘ.ተ.) ፣ በእርግዝና ጊዜ ሲጋራ፣ አልኮአል እንዲሁም አደንዛዥ እጾችን መጠቀም ፣ እና በወሊድ ጊዜ የሚያጋጥም የጽንስ መታፈን በሕፃኑ አእምሮ እድገት ላይ ተጽዕኖ አሳድረው ይህን ችግር ሊያመጡ ይችላሉ። ከዘረመል ጋር በተያያዘ ችግር፣ እንዲሁም በኢንፌክሽን እና በተለያዩ ህመሞች የተነሳም ሊከሰት ይችላል። ከ እድሜ ጋር ተያይዞ እንዲሁም በተለያየ ምክንያት እንደ አልዛይመር፣ እና ዲመንሽያ አይነት ህመሞች ይህንን አእምሮአዊ አካል ጉዳት ሊያስከትሉ ይችላሉ። አልኮል እና አደንዛዥ እጽ መጠቀምም ነርቭን ስለሚጎዱ ፤ ለ አእምሮአዊ አካል ጉዳተኝነት ያጋልጣሉ።
ቀደም ብሎ ምርመራ አድርጎ አስፈላጊውን ህክምና ክትትል በማድረግ አእምሮአዊ የአካል ጉዳትን መከላከል ይቻላል። አስፈላጊው የትምህርት እና የህክምና ድጋፍ ከተደረገላቸው፣ በዘርፋቸው እጅጉን የላቀ ደረጃ ሊደርሱ ይችላሉ።ትምህርት ቤቶችም ክፍሎቻቸውን እንደዚህ አይነት ልዩ ፍላጎት ላላቸው ህጻናት በማስተካከል ፣ ልዩ ልዩ የመማሪያ መሣሪያዎችን በማዘጋጀት እነኝህ ህጻናት የላቀ ደረጃ እንዲደርሱ ማድረግ ይቻላሉ።
አካል ጉዳተኝነት ጋር የተያያዘ የግንዛቤ ጉድለቶች
የአካልጉዳተኛ ሰዎችን እንዴት መደገፍ እንዳለብን ፤ እንዴትስ እነሱን ያካተተ ማህበረሰብ መገንባት እንደሚቻል ብዙ ሰው አያቅም። በዚህም የትነስ የአካል ጉዳተኝነት በማህበረስቡ ውስጥ በተሳሳተ መንገድ ይተረጎማል። ይህንንም ለመፍታት በግልጽ መነጋገርን አስፈላጊ ነው።

አንዳንድ የማህበረሰብ ክፍል የአካል ጉዳተኝነት እንደ ጎዶሎነት ታስቦ ፤ የአንድን ግለሰብ ያለውን ማህበረሰባዊ ጠቀሜታ የሚያሳንስ ተደርጎ ይወሰዳል። እውነታው ግን ከዚህ የራቀ ነው። የአካል ጉዳት የአንድን ሰው ዋጋ አይገልጽምም/አይቀንስም። በቅጽበታዊ አጋጣሚ በተፈጠረ ክስተት አካል ጉዳተኛ ብንሆን ፤ ማንነታችን/ ዋጋችን አይለወጥም። አካል ጉዳተኞች ከማንኛውም ሰው እኩል በተለያዩ ዘርፎች ተወዳዳሪ መሆን ይችላሉ ። ለምሳሌ አንድ የ ዩንቨርስቲ ፕሮፌሰር ባጋጠመው አደጋ/ ህመም ከወገብ በታች ፓራላይዝድ ቢሆን፤ እንቅስቃሴው ከመገደቡ ባሻገር የሚያስተምረው ትምህርት ሆነ፤ የሚያደርገው የጥናታዊ ጽሁፍ ጥራት ላይ ለውጥ አይኖረውም። ለዚህም ነው እንደ ስቲፈን ሃውኪንግ ያሉ የአካል ጉዳተኞች በዘመናቸው ምርጥ ሳይንቲስት ተብለው፤ ለዘመናት ያስቸገሩ ችግሮችን ፈትተው፤ ለሰው ልጅ በሙሉ ተገዳዳሪ የሌለው አስተዋእጽ አድርገው ያለፉት።
የተቀረው የማህበረሰብ ክፍል ደግሞ ለአካል ጉዳተኞች ሀዘኔታ ይሰማዋል ። ይህ ከመልካምነት የመነጨ ቢሆንም አይመከረም። አካል ጉዳተኞችን ያለባቸውን ሁኔት መረዳት እንጂ፤ ማዘን ትክክል አይደለም። በተለምዶ ሀዘን የሚሰማን ለተጎዳ፣ ከ እኛ የከፋ ስፍራ ላለ፣ ወይም የሆነ ነገር ጎድሎበታል ብለን ለምናስበው ሰው ነው። ይህ ደግሞ አካል ጉዳተኞችን አይወክልም። እንደውም አሉታዊ ተጸእኖ ነው ያለው። ይህም ያላቸውን የሞራል ልዕልና ከመስረቁም ባሻገር፣ እራሳቸውን በራስ የመቻል ተነሳሽነታቸውን ያመነምናል።
ለዚህም አካል ጉዳተኞች የማህበረሰባችን እጅግ ጠቃሚ አካል መሆናቸውን መረዳት ይኖርብናል።
መፍትሔው እና ነባራዊ ሁኔታ

የህክምና አማራጮችን ከላይ የዘረዘርን ቢሆንም፤ መፍትሔው ህክምና ላይ አያበቃም። የምንኖርበትን ነባራዊ አለምም እነሱን ያገናዘበ ሊሆን ይገባል። የሚገነቡ ህንጻዎች፣ የምንንቀሳቀስባቸው መንገዶች ለአካል ጉዳተኞች የሚሆን የመጓጓዣ አማራጭ ሊኖራቸው ይገባል። የማህበረሰባቸን አካል እንደመሆናቸው አኗኗራቸንም እነሱን ያካተተ መሆን አለበት።
በሀገራችን በአካል ጉዳተኝነት ዙሪያ በግልጽ መነጋገር ስለተጀመረ፣ መልካም ለውጦች መታየት ጀምረዋል። ተፈጻሚነታቸው ጥያቄ ውስጥ ቢገባም ፣ በመንግስት በኩል ለአካል ጉዳተኝነት የህግ ማዕቀፍ ውጥቶለታል። በዚህም ዙሪያ እየሰሩ የሚገኙ ብዙ ግለሰቦችም እንዲሁም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችም አሉ።
ይህ መልካም ለውጥ ቢሆንም፣ እጅግ ብዙ መንገድ ገናይቀረናል።
ዋናው ነጥብ
የአካል ጉዳት አሳዛኝ አይደለም። ይህ የአካል ጉዳተኛ የሆኑ ሰዎች ያላቸውን ጥንካሬና አቅም ባለመገንዘብ ላይ ነው።
ከህክምና ባሻገር አኗኗራችን እንዲሁም አከባቢያችን እነሱን ያካተተ መሆን ይኖርበታል።
ሁሉን ያካተተች የተሻለች ኢትዮጵያን እንገንባ!
Comments